tg-me.com/Getem_lemitemaw/643
Last Update:
📜📜ከመጽሐፍት አምድ📜📜
እመጓ ከዶ/ር አለማየሁ
አንድ ተመራማሪ ለአንድ መንፈሳዊ አባት እንዲህ የሚል ጥያቄ አቀረቡለት
አባ ለምንድ ነው ታሪካችሁ ምሥጢር ፤ መድኃኒቱን ምሥጢር ፤ ቅርሱን ሁሉ ምሥጢር ማድረግ ምን ይጠቅማል ።
እኛስ የክርስቶስ ፍቅር የለንምን የቃል ኪዳኑ በረከት አይገባንም እጅግ ምሥጢራዊ ከመሆናችሁ የተነሣ ከትውልዱ ጋር የሚያገናኝ የቅብብሎሽ ድልድይ መሥራት አልቻላችሁም ።
ሁሉ ነገር ምሥጢር ማድረግ ምን ይጠቅማችሁኋል ምን አለ ሁሉንም ነገር ትውልዱ ቢያውቀው ?
አባ መለሱ፦ በአፍላ ትጀምራላችሁ በወረት ትተውታላችሁ ። ያወቃችሁትን ትረሳላችሁ ፤ ያላወቃችሁትን ለማወቅ ትጥራላችሁ ፤ የያዛችሁትን ትረግጣላችሁ ፤ የረገጣችሁትን ትይዛላችሁ ።
ምኞታችሁ ልክ የለውም ፤ አምሮታችሁ ብዙ ነው።
የአማራችሁን ስታገኙ ወዲያው ይሰላቻችኃል። ተው የተባላችሁትን ትሽራላችሁ ፤ የተከልከላችሁትን ትደፍራላችሁ ፤ የተፈቀደላችሁን ችላ ትሉታላችሁ። ሁሉን ማወቅ ትፈልጋላችሁ ፤ በአንዱም ግን አትጠቀሙበትም ። ሁሉ አላችሁ ፤ ግን ባዷችሁን ናችሁ። ሃይማኖት እንጂ (እምነት) የላችሁም ።
መቀመሚያውን ነግሬህ ማርከሻውን ሳልገልጥልህ መጀመሪያውን ብቻ ሞጭልፈህ ትተኸኝ ትሄዳለህ ። ጥበብን "ሀ ግእዝ ብዬ ላስተምርህ ብሞክር ፤ መንደር ውስጥ በቃረምካት ዕውቀት ተመክተህ በመሰልቸት "ሆ ሳብዕ ብለህ ቀድመህ ትዘጋዋለህ ።
የግል ታሪካችሁ ቢታይ ወጥነት የጎደለው ከዚህም ከዚያም የተለከፈከፈ የተማሪ ኮፋዳ ውስጥ ያለ እህል ይመስላል።
ተምራችሁ እውቀት ስታገኙ ፤ ሰርታችሁ ሀብት ስታፈሩ ፤ ከላይ የሆናችሁትን ሀገር ለቃችሁ ፤ ሰፋ ወዳለው እንሂድ ብላችሁ እንደገና ከታች ፤ ትጀምራላችሁ ትቀጥላላችሁ ፤ በመጨረሻም ከጀመራችሁበት ትገኛላችሁ።
@Getemlemitemaw
@Getem_lemitemaw
BY ግጥም ለሚጠማዉ
Share with your friend now:
tg-me.com/Getem_lemitemaw/643